በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን  

 እንኳን ከዘመነ ማርቆስ ወደ ዘመነ ሉቃስ በሰላም አደረሳችሁ! አደረሰን!

                      “በቸርነትህ ዓመታትን ታቀዳጃለህ” መዝ ፷፬፥፩

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰሜን አሜሪካ አኅጉረ ስብከት የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጉባኤ እንኳን ከዘመነ ማርቆስ ወደ ዘመነ ሉቃስ በሰላም አደረሳችሁ በማለት ልባዊ ምኞቱን ሲገልጽ በታላቅ ደስታ ነው።

በሰው ጥረት ሳይሆን አምላካችን በቸርነቱ እና በፍቅሩ የገባልንን ቃል ኪዳን በማሰብ ዘመናትን እያፈራረቀ ዛሬ ለደረስንባት ዕለት በሰላም በጤና ስላደረሰን ከምስጋና በቀር ምንም ማድረግ አይቻለንምና እንደ መላዕክቱ “ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ የሠራዊት ጌታ ልዑል እግዚአብሔር ምድር ሁሉ ከክብርህ ተሞልታለች”(ኢሳ ፮፥፫) ብለን ምስጋናችንን እናቀርባለን። አባታችን ኖኅ ከጥፋት ውኃ በኋላ እግዚአብሔር ለዘር እንተርፍ ዘንድ እርሱንና ቤተሰቦቹን ጠብቆ እንዲሁም ከፍጥረታቱ መካከል አምላካችን ዓለምን ሲፈጥር “ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው” እንዳለ በኖኅ ጊዜ በነበረው የውኃ ጥፋትም ወደ መርከቧ ወንድና ሴት እያደረገ አራዊትንና እንስሳትን እንዲሁም በሰማይ የሚበሩትን ሁሉ ለዘር ማትረፉ ይታወቃል። አባታችን ኖኅም የምስጋና መሥዋዕቱን ለእግዚአብሔር አቅርቦ ተቀባይነትን ስላገኘ በቅዱስ መጽሐፍ እንዲህ የሚል ቃል ኪዳን ለሰው ልጆች ተሰጥትዋል፦ Read more

በኢ/ኦተ/ቤ/ክ በሰሜን አሜሪካ አኅጉረ ስብከት የሰንበት ትቤቶች አንድነት ጉባኤ

22 ተኛው ዓመታዊ ጉባኤ በርእሰ አድባራት ጽርሐ አርያም ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል አርብ ነሔሴ 27 ከምሽቱ 6:00 pm ተጀመረ።

የደብሩ (የካቴድራሉ) አስተዳዳሪ መልአከ አርያም አባ ኃይለ ሚካኤል

መልአከ ሰላም ቀሲስ መስፍን (ዶ/ር) እንዲሁም ሌሎች አባቶች እና ከየክፍለ ከተማው የመጡ የሰ/ት/ቤት አባላት በተገኙበት በሠርክ ጸሎት መርሃ ግብሩ ተጀምሯል።

በማስከተልም “ህየንተ አበውኪ ተወልዱ ለኪ ደቂቅ”   

“በአባቶች ፈንታ ልጆች ተወለዱልሽ” መዝ 44፥16

የሚለው ምስባክ ተሰብኮ በማስከተልም በርእሰ ደብር ብርሃኑ አካል

“እነሆ የጠራኸኝ” 1ኛ መ ሳሙ 3፥5

በሚል ኃይለ ቃል ትምህርት አስተላልፈዋል።

የሰ/ት/ቤቱ ሊቀ መንበርም የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክት አስተላልፈዋል።

ላለፉት 3 ዓመታት በመላው ዓለም በተከሰተው ወረርሽኝ ምክንያት ጉባኤውን በአካል ማድረግ ባይቻልም ዘመኑ የፈጠረውን የመገናኛ ዘዴ በመጠቀም ዓመታዊ ጉባኤው ተካሂዷል።

እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በ2014 ዓ/ም አንድነት ጉባኤው በተመሠረተበት ቤዛ ኩሉ ሰ/ት/ቤት አዘጋጅነት ለሚቀጥሉት 3 ቀናት ጉባኤው የሚቀጥል ሲሆን የዕለቱን ክንውኖች እየተካታተልን የምንዘግብ መሆናችንን እንገልፃለን።